የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምእመናን የምትመራባቸው ሦስት የትምህርት መመሪያዎች አሏት፡፡ እነርሱም፡-
ሀ. ዶግማ፡- ቃሉ የግሪክ ሲሆን ትርጉሙም የማይለወጥ፣ የማይቀየር የማይሻሻል፣ የማያረጅ ማለት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል ሁሉ ዶግማ ነው፡፡
ምሳሌ፤ አስርቱ ትእዛዛት ፣ስድስቱ ቃላተ ወንጌል፣ አምስቱ አዕማደ ምስጢር፡፡ ዶግማ የእግዚአብሔር ቃል ስለሆነ ሰው እንደፍላጎቱ እንደምኞቱ ሊጨምርበት፣ ሊቀንስበት ወይም ሲያሸሽለው አይችልም፡፡ 2ኛ ጴጥ 1.20፣ ዕብ 1.1-3 ፣ ማቴ 24.35
ለ. ቀኖና፡- እንደ ዶግማ የግሪክ ቃል ነው፡፡ የቃሉ አመጣጥ ‹‹ሸንበቆ›› ከሚለው ነው፡፡ የጥንት አባቶች ሸንበቆን ርዝመት መለኪያ አድርገው ይጠቀሙበት ነበር፡፡ እንደዚሁም ሁሉ የክርስቲያኖች ሥርዓታዊ ሕይወት መለኪያ ሆኖ እንዲያገለግል የቤተክርስቲያ አባቶችና ሊቃውንት በጉባዔ ወይም በሲኖዶስ የሚወስኑት ውሳኔ ቀኖና ይባላል፡፡
ቀኖና እንደወቅቱና ጊዜው በሲኖዶስ ሊለወጥ ወይም ሊሻሻል ይችላል፡፡የቀኖና ምሳሌዎች ጾም ዶግማ ሲሆን የጾም ጊዜ ቀኖና ነው፡፡ ቅዳሴ ዶግማ ሲሆን የቅዳሴ ጊዜ ቀኖና ነው፡፡
እግዚአብሔር ሁሉን በሥርዓት ያደርጋል፡፡የእጁ ፍጥረታት የሆኑት መላእክትና ሰው በሥርዓት እንዲያመልኩት ሕግና ሥርዓቱን እዲጠብቁ ይፈልጋል፡፡ 1ኛ ቆሮ 11.34፣ 1ኛ ቆሮ 14.40፣ ቆላ 2.5 የሐዋ.ሥራ 16.4፣ 2ኛ ተሰ 3.6፣ 1ኛ ቆሮ 12.2
ሐ. ትውፊት፡- ‹‹አወፈየ›› ከሚለው የግእዝ ገስ የወጣ ሲሆ ትርጉሙም ውርስ፣ ውርርስ፣ ርክክብ፣ ቅብብል ማለት ነው፡፡ ይኸውም አንድ ትውልድ ከእርሱ በፊት ከነበሩት የሚወርሰው የሚያገኘውና የሚቀበለው ነገር ነው፡፡ ሂደቱም በዚህ የሚያበቃ ሳይሆን እርሱም በተራው ለተተኪው ያስተላልፋል፡፡ ትውፊት ቅዱሳት መጻሕፍት ከመጻፋቸው በፊት የነበረ ነው፡፡