ዐቢይ ጾምአትምኢሜይል
 የካቲት 13 ቀን 2006 ዓ.ም.
ሊቀ ጉባኤ ቀለመ ወርቅ ውብነህ

ጾም ማለት መተው መከልከል ማለት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት ሠርታ ጾመን ከአምላካችን ጋር ህብረት እንዲኖረን ፤መንፈሳዊ ኃይል እንድናገኝ አድርጋለች፡፡ ጾም በእግዚአብሐር የተቀደሰ ስለሆነ ወደ ቅድስና ጎዳና የሚመራ ነው፡፡

በጾም ወራት ከመባልዕት መከልከል ብቻ ሳይሆን ዐይን ክፉ ከማየት አንደበት ክፉ ከመናገር ጆሮ ክፉ ከመስማት መቆጠብ እንደሚገባ ተጽፎአል፡፡ “ይጹም ዐይን፣ ይጹም ልሳን፣ እዝንኒ ይጹም እምሰሚዓ ኀሡም በተፋቆሮ” /ቅዱስ ያሬድ ጾመ ድጓ/፡፡ በጾም ወራት፣ ላምሮት፣ ለቅንጦት፣ የሚበሉ ወይም ለመንፈሳዊ ኃይል ተቃራኒ የሆኑ ሥጋዊ ፍትወትን የሚያበረታቱ፣ ሥጋንና የሚያሰክሩ መጠጦችን /ዳን.10፥2-3/ ቅቤና ወተትን ማራቅ ታዟል፡፡ /መዝ.108፥24፣ 1ቆሮ.7፥5፣ 2ቆሮ.6፥6/

በብሉይ ኪዳን ጾም ከፍተኛ ቦታ አለው፡፡ የብሉይ ኪዳን ነቢያት ከእግዚአብሔር በሚገናኙበት ወራት እህልና ውኃ በአፋቸው አይገባም ነበር፡፡ /ዘፀ.34፥28/አስቴር አስቀድማ ሦስት ቀን ጾማ ጸልያ በእስራኤል ላይ የመጣውን መቅሰፍት እንዲመለስ አድርጋለች፡፡አስ4፡15-16 በኃጢአት ብዛት የታዘዘው የእግዚአብሔር መዓት የሚመለሰው ሕዝቡ በጾም ሲለምኑትና ሲማልዱት ነበር፡፡ /ዮና.2፥7-10/

በሐዲስ ኪዳንም ጾም ሰው ሠራሽ ሕግ ሳይሆን እራሱ ክርስቶስ የሥራ መጀመሪያ አድርጎ የሠራው ሕግ ነው፡፡ /ማቴ.4፥2፣ ሉቃ.4፥2/ ይህም ብቻ ሳይሆን በቁራኝነት ተቆራኝቶ አብሮ የሚኖር መንፈሰ ርኩስ ሰይጣን እንኳን በጾም የሚወገድ መሆኑን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተናግሮአል፡፡ ማቴ.17፥21፣ ማር.9፥2

ቤተ ክርስቲያንን እንዲያገለግሉ የታዘዙ ሐዋርያትም በየጊዜው ከመንፈስ ቅዱስ ትእዛዝ የሚቀበሉት በጾም በጸሎት ላይ እንዳሉ ነበር፡፡ /የሐዋ.ሥራ.13፥2/ ለስብከተ ወንጌል የሚያገለግሉ ዲያቆናትና ቀሳውስትም የሚሾሙት በጾምና በጸሎት ነበር፡፡ /የሐ. ሥራ.13፥3፣ 14፥23/ እነቆርኔሌዎስ ያላሰቡትን ያዩና ያገኙ የነበረው በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን ማልደው ነው፡፡ /የሐ. ሥራ.10፥30/

ዐቢይ ጾምም ቤተክርስቲያናችን እንድንጾም ካወጀችልን ጾም አንዱ ነው፡፡ዐቢይ ጾምየተለያዩ ስሞች አሉት፡፡ አንደኛ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው የአርባ ቀን ጾም በመሆኑ እንዲሁም ዐቢይ እግዚአብሔር ወዓቢይ ኀይሉ ዓቢይ እግዚአብሔር ወብዙኃ አኰቴቱ የተባለ ጌታ የጾመው ስለሆነ፣ /መዝ.47፥1፣ መዝ.146፥5/፡፡ ሁለተኛ ሁዳዴ ጾም ይባላል፡፡ ይህም የመንግሥት እርሻ ወይም ማንኛውም የሕዝብ ብዛት ያለበት ሥራ ሁዳድ ስለሚባል ሲሆን ከአጽዋማት ሁሉ ብዙ ቀናት ስለሚጾምና ኃያሉ አምላካችን ስለጾመው ነው፡፡፣ /አሞ.7፥1/፡፡ ሦስተኛ በዓተ ጾም ይባላል፡፡የጾም መግቢያ፣ መባቻ ወይም ጾሙ የሚሰፍርበት በዓት ማለት ነው፡፡ አራተኛ ጾመ አርባ ይባላል፡፡ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጾመው 40 /ዓርባ/ ቀን ስለሆነ፣ /ማቴ.4፥1/ አምስተኛ ጾመ ኢየሱስይባላል፡፡ ጾሞ፣ ጹሙ ብሎ ስላዘዘን፣ ስድስተኛ ጾመ ሙሴ ይባላል፡፡ ቅዱስ ያሬድ በዘወረደ ሰኞ ዕዝል ከመዝ ይቤ ሙሴ እስመ ለዓለም፣ ሙሴኒ ይቤ በውስተ ኦሪት እያለ በጾመ ድጓ ስለ ዘመረ ነው፡፡

ዐቢይ ጾምጌታ ከተጠመቀ በኋላ የጾመው የአርባ ቀን ጾም ነው፡፡ ማቴ.4፥1 ምእመናን ጌታቸው ያደረገውን ምሳሌ ተከትለው ይጾሙታል፡፡ ዐቢይ ጾም ስምንት ሳምንታት /55 ቀኖች/ አሉት፡፡ ሰባት ቅዳሜ ስምንት እሑድ ይገኛሉ፡፡ አሥራ አምስት ቀን ማለት ነው፡፡ ከጥሉላት እንጂ ከእህል ውኃ ስለማይጦሙ የጦሙ ወራት አርባ ቀን ብቻ ይሆናል፡፡